የሩሲያና ቻይና ጥምረት ያሠጋቸው የፈረንሣይ ዕጩ ፕሬዚዳንት ማሪን ላ ፔን

 


(ኦርጂን)

በተጠባቂው የፈረንሣይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ፕሬዚዳንት ኢማኑኤል ማክሮንን የሚገዳደሩት ማሪን ፔን፣ ሩሲያ ትልቅ አቅም ያላት አገር በመሆኗ አውሮፓ በዲፕሎማሲያዊ መንገድ ሊያቀርባት ይገባል ሲሉ ሐሳባቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

የሩሲያና የዩክሬን ጦርነት ሁለት ወራትን ቢያስቆጥርም፣ የምዕራቡ ዓለም ጦርነቱን ለማስቆም ከሚያደርገው ጥረት ይልቅ የውክልና ጦርነቱን በዩክሬን ምድር ማድረግን መርጧል፡፡

በውክልናና በቃላት ጦርነት ውስጥ ያሉት ሩሲያና ምዕራባውያን ከገቡበት ጦርነት እንዲወጡ ቱርክ፣ ሩሲያንና ዩክሬንን ማደራደር ብትጀምርም፣ እስካሁን ለውጥ አላመጣም፡፡ በዩክሬንም ጦርነቱ ቀጥሎ ሩሲያ ቁልፍ የተባሉ ቦታዎችን እየተቆጣጠረች ነው፡፡ ዘመን አመጣሽ መሣሪያዎችን ከለት ዕለት እያስተዋወቀችም ነው፡፡

ሩሲያን እንደ ሊቢያ፣ አፍጋኒስታን፣ ኢራቅ፣ ሶሪያና ሌሎችም አገሮች አድርጎ መቁጠር አደጋው ለዓለም ይተርፋል ሲሉ በዩክሬንና ሩሲያ መካከል ጦርነቱ ሳይጀመር ሲወተውቱ የነበሩ አንዳንድ የምዕራባውያን ምሁራን ሰሚ አጥተውም ዓለም ለማኅበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ቀውስ ተጋልጣለች፡፡

ኮቪድ-19 በዓለም ላይ የፈጠረው ጫና ሳያባራ፣ የሩሲያና ዩክሬን ጦርነት መቀስቀሱ ላደጉትና ለዩክሬን ወግነው መሣሪያና ገንዘብ ለሚያቀርቡት ምዕራባውያንም አልበጀም፡፡

ምዕራባውያን የሩሲያን የነዳጅ አቅርቦት ጨምሮ የተለያዩ የኢኮኖሚ ማዕቀብ ቢጥሉም፣ ሩሲያ ከቻይና ጋር ያላት ትስስር ለምዕራባውያኑ ሌላ ፈተና ይዞ እንደሚመጣ  የፊታችን እሑድ ሚያዝያ 16 ቀን 2014 .. በፈረንሣይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ማክሮንን ይገዳደራሉ የተባሉት ማሪን ፔን ተናግረዋል፡፡

በመጀመርያው ዙር የፈረንሣይ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ የወቅቱ የፈረንሣይ ፕሬዚዳንት አማኑኤል ማክሮን ካስመዘገቡት 27.8 በመቶ ድምፅ በመቀጠል 23.1 በመቶ ድምፅ ያገኙት ፔን፣ ከሁለተኛው ምርጫ አስቀድሞ ከፍራንስ ብሎ ኖርማንዴ ሬዲዮ ጣቢያ ጋር በነበራቸው ቆይታ፣ የኢኮኖሚና የጦር ኃያላኖቹ ሩሲያና ቻይና ከመጣመራቸውም በፊት አውሮፓውያን ሩሲያን በዲፕሎማሲ ማቅረብ አለባቸው ብለዋል፡፡

ፔንን አስመልክቶ አርቲ እንደዘገበው፣ የኢማኑኤል ማክሮን ተቀናቃኝ ማሪን ፔን የሞስኮ እና የቤጂንግ ጥምረት አውሮፓን አደጋ ላይ ይጥላል፡፡

‹‹የሩሲያና የቻይና ጥምረትን ማስቆም እንደሚፈልጉ የሚናገሩት ላፔን፣ ትልቅ አቅም ያላት ሩሲያ ከቻይና ጋር አንድ መሆን የዓለም ግንባር ቀደም የኢኮኖሚና የመከላከያ ኃይል ይፈጥራል ይህንንም አውሮፓውያን በዲፕሎማሲ ሊያስቀሩት ይገባል›› ብለዋል፡፡

ሩሲያን ከቀረው አውሮፓ ጋር መቀላቀል የፈረንሣይ ሕዝብንና አጠቃላይ የአኅጉሩን ሰላም ለማስጠበቅ እንደሚያስችልም አክለዋል፡፡

‹‹ሩሲያ ትልቅ አቅም እንዳላት አስባለሁ፡፡ እናም በስተመጨረሻ ከቻይና ጋር ጥምረት እንድትፈጥር አልፈልግም፤›› የሚሉት ፔን፣የሩሲያን ፖለቲካ ከአውሮፓ ጋር መልሶ ማዋሃድ ያስፈልጋል፣ ይህ የአኅጉሪቱንና የፈረንሣይ ደኅንነትን ለማረጋገጥ ዋስትና ነው፤የሚለውን የማክሮን ንግግር የሚደግፉት ፔን፣ የአገር መሪ ወይም መንግሥት አጭር ዕይታ የለውም የወደፊቱን ማየት አለበት ብለዋል፡፡

‹‹በዓለም ሰፊ የቆዳ ስፋት ያላት አገር በዓለም ቀዳሚ የሕዝብ ቁጥር ካላት አገር ጋር ትብብር ለመፍጠር ስትሠራ ሁኔታውን ለማስቆም ምንም አላደረግንም፡፡ በዓለም የጥሬ ዕቃ አምራች ቀዳሚ አገር የሆነችው ሩሲያ በዓለም ትልቁ የፋብሪካዎች ባለቤት ከሆነችው ቻይና ጋር ስትዋሃድ ዝም ብለን ካየን በዓለም ቁጥር አንድ የመከላከያ አቅም ሲገነባ እንደፈቀድን ይቆጠራል፡፡ በመሆኑም ዲፕሎማሲያዊ ዕርምጃ መውሰድ አለብን፡፡ ጦርነቱ አብቅቶ የሰላም ስምምነት ሲደረግም፣ 21ኛው ክፍለ ዘመን ለዓለም ሥጋት ሊሆን የሚችለውን የሩሲያና የቻይናንን ጥምረት ማስቀረት ይገባል፤›› ብለዋል፡፡

ሩሲያ የዩክሬንን ሉዓላዊነት መንፈግ የለባትም፡፡ ነገር ግን ... 2014 በክራይሚያ ውሳኔ ሕዝብ (ሪፈረንደም) ተካሄደ እንጂ ጦርነት አልተካሄደም፣ ሩሲያንም ማግለል የለብንም በሚለው አቋማቸው የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን ደጋፊ ተደርገው የሚወሰዱት እኚህ ሴት፣ የአውሮፓ ኅብረትን ያፈራርሳሉ ተብለው በተቀናቃኞቻቸው ይተቻሉ፡፡ የአውሮፓ ኅብረትም ቢሆን ስለ ሴትየዋ የምረጡኝ ቅስቀሳ ዘመቻ ብዙም የተናገረው የለም፡፡

... 2017 በተሳተፉበት ምርጫ ፈረንሣይን ከመሠረተችው የአውሮፓ ኅብረት የማስወጣት ዓላማ የነበራቸውና በኋላ ደግሞ በዩሮ ከመገበያየት ማስወጣት ያስፈልጋል የሚል አቋም ያመጡት ፔን፣ ለአውሮፓ ኅብረት መፍረክረክ ምክንያት ሊሆኑ ይችላሉም ተብሏል፡፡

የላ ፔን ስትራቴጂ እንደ ብሪታኒያው ‹‹ብሪኤግዚት›› የፈረንሣይ ‹‹ፍሪኤግዚት›› ነው የሚሉት ተቀናቃኞች፣ ፈረንሣይ የአውሮፓ ኅብረት አባል ሆና ብትቆይም እንኳን  የራሷ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊና የኢሚግሬሽን ፖሊሲ እንደሚኖራትና እሳቸውም የፈረንሣይን ሉዓላዊነት እንደሚያቀነቅኑ ዘጋርዲያን አስፍሯል፡፡

በላ ፔን ዕቅድ መሠረት በዜግነት፣ በማንነትና በኢሚግሬሸን ሕግ ላይ ውሳኔ ሕዝብ የሚካሄድ ይሆናል፡፡ ይህ የሕገ መንግሥት ማሻሻያ የሚጠይቅና ለሥራ ቅጥር፣ ለደኅንነት ጥቅማ ጥቅሞችና ለመኖሪያ ቤት ቅድሚያ ለፈረንሣይ ዜጎች የሚያሰጥ በመሆኑ፣ ከአውሮፓ ኅብረት እሴትና በነፃ የመንቀሳቀስና የመሥራት ሕግ ጋር የሚፃረር ይሆናል፡፡

በአውሮፓ ኅብረት አባል አገሮች ሕዝቦች መካከል ያለውን በነፃነት የመንቀሳቀስ መብት በተመለከተም፣ የድንበር ቁጥጥሩን መልሰው እንደሚያዋቅሩት፣ የአውሮፓ ኅብረትንና የሻንጋይ ሕጎችን ያልተከተሉ ወደ ፈረንሣይ የሚገቡ ዕቃዎችንና ሰዎችን እንደሚቆጣጠሩ፣ ፈረንሣይ ለአውሮፓ ኅብረት የምትሰጠውን በጀት እንደሚቀንሱ ነው ያስታወቁት፡፡

በአኅጉሪቱ ያሉ ቀውሶችንና የአየር ንብረት ለውጥን አልታደገም በማለት የአውሮፓ ኅብረትን በመውቀስ የሚታወቁት የአውሮፓ ኅብረት ኮሚሽን የቀድሞ ባለሥልጣን ጆርጅ ሪክልስ ‹‹ ፔን የፈረንሣይ ፕሬዚዳንት ከሆኑ የአውሮፓ ኅብረት ይሽመደመዳል፤›› ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

(ጥንቅር በምሕረት ሞገስ)

ይህን ተጭነው በቴለተግራም ገጽ ይቀላቀሉ ፤

 

Post a Comment

አዲስ የድሮ