ብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ በመረጃና ደኅንነት አመራር የሰለጠኑ የደቡብ ሱዳን የደህንነት ተቋም አባላትን አስመረቀ

የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ከደቡብ ሱዳን አቻው ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ ጋር በትብብር ለመስራት በደረሰው ስምምነት መሰረት ለሀገሪቱ የደኅንነት ተቋም አመራሮች በከፍተኛ የመረጃና ደህንነት አመራር ኪነሙያ ስልጠና በመስጠት አስመርቋል፡፡

 በአገልግሎቱ ስር በሚገኘው ብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ስልጠና የወሰዱት የደቡብ ሱዳን የደኅንነት ተቋም አባላት የምረቃ ሥነ ስርዓት ተካሂዷል።

በስ ስርዓቱ ላይ የተገኙት የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጀነራል አቶ ተመስገን ጥሩነህ የሁለቱ ሀገራት የደህንነት ተቋማት በመረጃ ልውውጥ፣ ሽብርተኝነትን በመዋጋት፣ ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎችን በመቆጣጠር እና ህገወጥ የገንዘብ ዝውውርን በመከላከል ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን በጋራ ሲሰሩ መቆየታቸውን አስታውሰዋል፡፡

አገልግሎቱ የጋራ የደኅንነት ስጋቶችን ለማስወገድ እንዲሁም ሰላምና ደህንነት ለማረጋገጥ ከቀጣናዊ፣ ከአህጉራዊና አለማቀፋዊ አቻ ተቋማት ጋር በትብብር እየሰራ መሆኑን የገለጹት አቶ ተመስገን፤ የደቡብ ሱዳን ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ አመራሮች በከፍተኛ የመረጃና ደህንነት አመራር ኪነ ሙያ ስኬታማ በሆነ መንገድ ስልጠናቸውን አጠናቅቀው ለምረቃ መብቃታቸው በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለው ጠንካራ ትብብር እያደገ መምጣቱን ያሳያል ብለዋል፡፡

ተመራቂዎቹም በቆይታቸው በመረጃ እና በአመራር ኪነ ሙያ ያገኙትን እውቀትም ወደ ተግባር በመቀየር ብዙ እንደሚጠበቅባቸው አመልክተዋል፡፡

ብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁን በምስራቅ አፍሪካ ብሎም በመላው አፍሪካ በመረጃና ደኅንነት ዘርፍ የልህቀት ማዕከል ለማድረግ እየተሰራ መሆኑን ያስታወቁት ዳይሬክተር ጀነራሉ፤ ሌሎች የአፍሪካ ሀገራትም ኦፊሰሮቻቸውን በተቋሙ ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላቸው ጠቁመዋል፡፡

የደቡብ ሱዳን ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ ዳይሬክተር ጀነራል ጀነራል አኮል ኮር ኩክ በበኩላቸው ሥልጠናው የተሳካ እንዲሆን ከፍተኛ ሚና ላበረከቱት የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት አመራሮች፤ ለብሔራዊ የመረጃና ደኅንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ መላው አባላት እንዲሁም ለሌሎችም የመንግሥት ባለሥልጣናት ላቅ ያለ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።

ኢትዮጵያ ለደቡብ ሱዳን እንደ ሀገር መወለድ ትልቅ አስተዋጽኦ ስላላት ለሀገሪቱ ህዝብና መንግሥት ከፍተኛ አድናቆት እንዳላቸውም የገለጹት የደቡብ ሱዳን ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ ዳይሬክተር ጀነራል፤ የ ሁለትዮሽ ግንኙነቱ በተለያዩ መስኮች ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል።

የብሔራዊ የመረጃና ደኀንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ፕሬዚዳንት አቶ ወንድወሰን ካሳ በመርሃግብሩ ላይ ባስተላለፉት መልዕክት ለምረቃ የበቁት የደቡብ ሱዳን ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ አመራሮች የተጣለባቸውን ከፍተኛ ሃላፊነት መወጣት የሚያስችል በመረጃና ደህንነት ኪነሙያ ያተኮረ ጥልቀት ያለው ስልጠና ማግኘታቸውን አመልክተዋል፡፡

የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም ከሰልጣኞች በተሰበሰበው ግብረመልስም ስልጠናው ወቅታዊ፣እጅግ ጠቃሚና ውጤታማ መሆኑ ታውቋል ብለዋል፡፡

ኢትዮጵያና ደቡብ ሱዳን የሚጋሩት በርካታ ጉዳይ መኖሩን የገለጹት አቶ ወንድወሰን፤ ሁለቱ ሀገራት ተመሳሳይ እጣ ፈንታና ሊለያይ የማይችል ትስስር አላቸው ብለዋል፡፡

አንዳንድ ሀገራት ፖለቲካዊ አለመረጋጋት አለ በሚል ሰበብ ዜጎቻቸው ከኢትዮጵያ ለቀው እንዲወጡ ግፊት ሲያደርጉ በነበረበት ወቅት ደቡብ ሱዳን ሰልጣኞችን መላኳም ይህን እንደሚያሳይ ገልጸዋል፡፡

በሁለቱ ሀገራት መካከል በመረጃና ደህንነት መስክ የተጀመረው ስልጠናም ተጠናክሮ እንደሚቀጥል አመልክተዋል፡፡

ከአራት ወራት በፊት የደቡብ ሱዳን ናሽናል ሴኩሪቲ ሰርቪስ ጀማሪ ኦፊሰሮች በብሔራዊ የመረጃና ደኀንነት ዩኒቨርሲቲ ኮሌጅ ስልጠና ወስደው መመረቃቸውን የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አገልግሎት ለኢዜአ በላከዉ መረጃ አመልክቷል፡፡

Post a Comment

አዲስ የድሮ